መጽሐፈ ሄኖክ
From Wikipedia, the free encyclopedia
መጽሐፈ ሄኖክ ጥንት የተጻፈ የመጽሐፍ ቅዱስ ዲዩትሮካኖኒካል መጽሓፍ ነው። በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን እምነት ዘንድ ይህም በሰዎች ቃላት በግዕዝ በያሮድ ልጅ በሄኖክ ከማየ አይህ አስቀድሞ ተጽፎ ነበር።
በመጽሓፉ ሄኖክ ከእግዚአብሔር ብዙ ራዕዮች ሲያይ ይናገራል። ደቂቀ ሴት (ትጉሃን) በአመጻቸው ጽናት ከቃየል ልጆች ጋራ አብረው እንዲዋሀዱ ከደብረ ቅዱስ በወረዱበት ጊዜ ሄኖክ እንደ ገሠጻቸው ይላል። የከለሱት ልጆቻቸውም በቁመት አብልጠው ረጃጅሞች እንደተባሉ እነዚህም አባቶቻቸውንና ምድሪቱን እንደ በደሉ ይላል። በሠሩት እጅግ ክፉ ሥራ ምክንያት የጥፋት ውኃ እንደሚደርሰባቸው ፈጽሞም እንደሚያሰምጣቸው የሚል የትንቢትም መጽሓፍ ነው። ይህም ትንቢት ኖህ በኖረበት ዘመን የተፈጸመ እንደነበረ የሚያምኑ ኣሉ።
በተጨማሪም ሄኖክ ወደ ሰማያት ተወስዶ የሰማይ ቦታዎችን ያሳዩታል። ከዚህ በላይ ስለ እግዚአብሔር መንግሥት ብዙ ይነበያል፤ ያኔ ጻድቃን ሺ ልጆችን ይወልዳሉና በሰላም በደስታ እንደሚኖሩ የሚል ትንቢት ነው። በዚህ መሠረት የመሢህ፣ የሙታን ትንሣኤ እና የዕለተ ደይን ትንቢቶች መጀመርያ ከሄኖክ ወይም ከአዳም ዘመን ጀምሮ ተገለጹ።
መጽሐፉ በሙላቱ የታወቀው በግዕዙ ትርጉም ሲሆን፣ የተጻፈበት ቋንቋ፡ በተለይም በኢትዮጵያ መምህራን ዘንድ፡ ግዕዝ መሆኑ ይታመናል። ከዚህም ውጭ የመፅሀፉ ፍርስራሽ ብራና ቅጂዎች እስራኤል በሚገኘው በሙት ባሕር ብራናዎች (በቁምራን ዋሾች) ውስጥ በአረማይስጥ ቋንቋ በ1950ዎቹ ተገኝቷል። ይህ መፅሀፍ በምዕራባውያን ምሁራንና ሊቃውንት ዘንድ መጀመርያ የተቀነባበረበት ልሳን ግዕዝ ሳይሆን አረማይስጥ ነው ተብሎ ይታመናል። ከዚህም በላይ አንዳንድ የግሪክኛ ወይም የሮማይስጥ ምንባቦች በከፊል ተርፈዋል።